በ22ኛው ዙር የፋና ላምሮት የድምፅ ውድድር 3ኛ ደረጃን ይዞ ላጠናቀቀው ወጣት ድምፃዊ ኤልያስ ገዛኸኝ በቦንጋ ከተማ አስተዳደር ደማቅ አቀባበል ተደርጓል።
በሥነ-ሥርዓቱ ላይ የተገኙት የካፋ ዞን አስተዳዳሪ አቶ እንዳሻው ከበደ እንደተናገሩት፣ ኤልያስ ለህዝብ በኪነ ጥበብ ዘርፍ የባህል እሴት ግንባታ ያበረከተው አስተዋጽኦ ከፍተኛ እንደሆነ ገልፀዋል ።
የአካባቢው ማኅበረሰብ በተፈጥሮው የታመመን የመጠየቅ፣ በደስታ አብሮ የመደሰት፣ በሞትና በችግር ጊዜ ደግሞ የመረዳዳትና የማዘን ትልቅ ባህላዊ እሴትና ፍቅር ያለው መሆኑንም ነው አቶ እንዳሻው።
አቶ እንዳሻው ወደፊት በሙዚቃው ዓለም ያሉ የጥበብ በሮች በራስ አቅም እና ጥበብ እንዲከፈቱ ተጨማሪ የብርታት ድምጽ ለመሆን የተዘጋጀ መሆኑን ገልጸው የእንኳን ደስ አለህ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
በዚህም በዞን መንግስት ስም የ300,000 ብር የገንዘብ ሽልማት ተሰጥቶታል።
የቦንጋ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ዶክተር ተክለዓብ ቡሎ በበኩላቸው በማንኛውም የህይወት ጉዞ ውስጥ ከባድ ፈተናዎች እና ተስፋ የሚያስቆርጡ ተራራዎች ሊገጥሙ እንደሚችሉ ጠቁመው፣ በእንደዚህ አይነት ወቅቶች “አለሁልህ፣ አይዞህ” የሚል አጋዥ ድምጽ ማግኘት ፈተናዎችን ወደ ሜዳ በመቀየር ህልምን ለማሳካት ትልቅ አቅም እንደሚሆን አስገንዝበዋል።
የኤልያስ ስኬት በራስ ጥረት ትልቅ ደረጃ መድረስ እንደሚቻል ለወጣቶች ያሳየ መሆኑን ገልጸው አካባቢውን ለማስተዋወቅ ላበረከተው አስተዋጽኦ ምስጋና አቅርበው ይበልጥ ጠንክሮ እንዲሰራ አሳስበዋል።
ድምፃዊው ለከተማዋ የገነባውን መልካም ስም በማድነቅ የ500 ካ.ሜ የመኖሪያ ቤት መስሪያ ቦታ ስጦታ አበርክተውለታል።
በዚሁ መርሃ ግብር ወጣቶችን ለማብቃት ላደረጉት አስተዋጽኦ መምህር ወሰናቸው አጥናፌ ከዞን መንግስት የ200,000 ብር እንዲሁም ከከተማ አሰተዳደር መንግስት የአንድ መቶ ሀምሳ ሺ ብር የገንዘብ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።
Source: FastMereja









No comments yet.