የኮሪደር ልማት ባሉ ዘንባባዎች ላይ የተተከሉ መብራቶችን የሰረቀ ተከሳሽ እጅ ከፈንጅ ይዞ በ6 ዓመት ከ6 ወር እስራት ማስቀጣቱን የየካ ክ/ከተማ ፖሊስ መምሪያ ገለፀ፡፡
#FastMereja I አላዛር ግሩም የተባለ ተከሳሽ ጨለማን ተገን በማድረግ የኮሪደር ልማት መብራቶችን ሰርቆ ሊሰወር ሲሞክር በቁጥጥር ስር የዋለው በየካ ክፍለ ከተማ ወረዳ 5 ኮከበ ጽባህ ት/ቤት አካባቢ ነው።
ግለሰቡ የዋጋ ግምቱ 202,800 ብር የሚያወጣ ንብረትነቱ የየካ ክፍለ ከተማ ወረዳ 5 ከተማ ውበትና ልማት ፅ/ቤት ክትትል እና ድጋፍ የኮሪደር ልማት የሆኑት ስድስት ስፖት ላይት መብራቶችን ሰርቆ ሊሰወር ሲል በአካባቢው በነበሩ የጸጥታ አካላት እጅ ከፈንጅ ሊያዝ መቻሉን የክ/ከተማው ፖሊስ መምሪያ ገልጿል።
ተከሳሹ ተይዞ ወደ ፖሊስ መምሪያው ከመጣ በኋላ በማስረጃ የተደገፈ ምርመራ በማጣራት በአቃቤ ህግ ክስ ሊመሰረትበት ችሏል፤ ፈጣን ችሎትም ቀርቦ ጉዳዩ ሲታይ ቆይቶ ተከሳሽ ላይ አስተማሪ ቅጣት ተወስኖበታል። የተከሳሽን መዝገብ የተከታተለው በፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት የካ ምድብ 1ኛ ወንጀል ችሎት አላዛር ግሩም ጥፋተኛ መሆኑን በማስረጃ በማረጋገጥ ተከሳሽን ያርማል ሌሎች ወንጀል ፈፃሚዎችን ያስተምራል በማለት 6 ዓመት ከ6 ወር እስራት እንዲቀጣ ውሳኔ አስተላልፎበታል።
የከተማዋ የልማት ስራዎች የእያንዳንዱ ዜጋ መጠቀሚያ እና ሀብት በመሆናቸው ጉዳት እንዳይደርስባቸው እና እንዳይሰረቁ በመከላከል ሁሉም ኃላፊነቱን እንዲወጣ እና ሲሰረቁ ወይም ጉዳት ሲደርስባቸው ሲያይ ለፖሊስ ጥቆማ መስጠት እንደሚያስፈልግ የአዲስ አበባ ፖሊስ መልዕክቱን ያስተላልፋል፡፡
#ችሎት
Source: FastMereja









No comments yet.