🙏
ራሷን ለእርሱ በሙሽርነት አሳልፋ ሰጥታለች
ራሷን የክርስቶስ ሙሽራ አድርጋ የለየች የፊቷ መልክ እጅግ ልዩ፣ ደምግባቷ ያማረ ነበረች እናታችን ቅድስት አርሴማ። የዲዮቅልጥያኖስ ታዛዥ የሆነው ንጉሥ ድርጣድስ ከሮሜ ሸሽታ በሔደችባት አብረዋት ከነበሩ ገዳማውያን ደናግል ጋራ ካሠራቸው በኋላ እናታችን ቅድስት አርሴማን ሚስቱ እንድትሆን በብዙ ሊያታልላት ሞከረ። እርሷ ግን በመንፈሳዊ ሕይወቷ ፍጹም ራሷን አሳልፋ የሰጠች፣ ራሷንም ለቸሩ አምላካችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ሙሽራ ያደረገች ናትና ለሰማያዊ ሙሽርነቷ የታመነች ሆነች። በኋላም እመ ምኔቷን እንድታባብላት ላካት፤ እመ ምኔቷ ግን “አይዞሽ! እንዲህ ላለው ምድራዊ ኃላፊ ነገር እንዳትታለይ፤ ሰማያዊ ሙሽርነትሽንና ንጽሕናሽን አጽኚ” ብላ ይበልጥ አጸናቻት።
ንጉሡም በግድ ይዟት ሊሄድ ቢል ኃይለ መንፈስ ቅዱስ አድሮባት ነበርና ያንን በጦር የጎለመሰ ሰውነት ያለውን ብርቱ ጦረኛ ከመሬት ፈጠፈጠችው። ንጉሡም እጅግም ተቆጥቶ ቅድስት አርሴማን አሠራትና ደናግሉን በፊቷ አንድ በአንድ አንገታቸውን ቀላቸው። እርሷ ግን “አይዟችሁ!” እያለች ታጽናናቸው ነበር። ይልቁንም ትሳቀቃለች ብሎ ባደረገው ነገር ቅዱሳኑ ሰማያዊ አክሊልን ሲቀበሉ ትመለከት ነበር። እርሷንም ሁለቱን ጡቶቿን ቆ ረጠ፤ ቀጥሎም ሁለቱን ዐይኖቿን አወጣቸው፤ በብዙ መከራም እጅግ አሠቃያት። ንጽሕት ድንግል እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ልዩ የብርሃን ዐይኖችን ሰጠቻት።
በመጨረሻም እርሷን ማሠቃየት ሲሰለች ከቀሩት ከሰባ አምስት ወንዶችና ከሃያ ሰባት ደናግል ሴቶች ጋራ መስከረም ሃያ ዘጠኝ ቀን አንገቷን ሰየፋቸውና የሰማዕትነትን የድል አክሊል ተቀዳጁ። ቅድስት አርሴማ በሰማዕትነት ስታርፍ ጌታችን ነፍሷን በክብር ተቀበላት ራሷን ለእርሱ በሙሽርነት አሳልፋ ሰጥታለችና ብዙ ቃል ኪዳንም ሰጣት፡፡
ዓለምን የናቁ ገዳማውያን የሚያገኙት ምድራዊ ክብር አያጓጓቸውም፣ ስጋዊ ድሎትና ምቾት አይማርካቸውም ራሳቸውን ለጌታቸው አሳልፈው ሰጥተዋልና፡፡ እኛም ገዳማቸውን ስንደግፍ በዓታቸውን ስናጸና ከበረከታቸው እንሳተፋለን፡፡
ድጋፍ ለማድረግ:- ሙትአንሳ ማር ቅዱሰ ሚካኤል አንድነት ገዳም
ኢትዮጲያ ንግድ ባንክ
1000442598391
ወይም
አቢሲኒያ ባንክ
141029444
ለበለጠ መረጃ:- 09 38 64 44 44/0918077957
Source: FastMereja









No comments yet.