ትብብር ለኢትዮጵያ አንድነት ወደ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ያለመግባት ውሳኔውን በድጋሚ ሊያጤነው እንደሚችል አስታወቀ

- Advertisement -
Sidebar AD

ኢሕአፓ እና እናትን ጨምሮ 4 ተፎካካሪ ፓርቲዎች የመሠረቱት ትብብር ለኢትዮጵያ አንድነት በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ወደ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለመግባት የሚያስችላቸውን ድምጽ ያገኙ እጩዎቹን ይዞ አዲሱ ምክር ቤት ያለመቀላቀል አቋሙን ድጋሚ አጢኖ ሊቀይረው የሚችለው ፖለቲካዊ ውሳኔ መሆኑን ለአሐዱ አስታውቋል።

የጥምረቱ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ጌትነት ወርቁ ከ”አሐዱ መድረክ” ጋር በነበራቸው ቆይታ አሁን ባለው ነባራዊ ሁኔታ ምክር ቤት ላለመግባት መወሰናቸውን ገልጸው፤ ውሳኔው ዘልዓለማዊ እንዳልሆነ እና ሂደቱ አዎንታዊ ለውጥ ካሳየ ውሳኔው ድጋሚ ሊመረመር እንደሚችል ተናግረዋል።

በምርጫ ሂደቱ ሙሉ እምነት ሳይኖር ምክር ቤት መግባት የመንግሥትን ሕጋዊነት ሙሉ በሙሉ መቀበል መሆኑን ያብራሩት አቶ ጌትነት ጥምረቱ በምርጫው ወቅት ከታጠቁ ኃይሎች፣ ከውጭ መገናኛ ብዙኃን እና ከዲያስፖራው የበረቱ ፈተናዎች እንዳስተናገደ ገልጸዋል።

ጥምረቱ አሁንም ቢሆን ለሰላማዊ ትግል እና ለድርድር ቅድሚያ እንደሚሰጥ፤ የምርጫ ሂደትና ሰላማዊ ትግል ከጦርነት አማራጭ ይልቅ አነስተኛ ዋጋ የሚያስከፍሉ መሆናቸውንም አክለው ገልጸዋል።

ጦርነት የሚያሳድረው ማኅበረ-ኢኮኖሚያዊ እና ሥነ-ልቦናዊ ተፅዕኖ በቀላሉ የማይጠፋ መሆኑን በሰሜን ኢትዮጵያ የታየውን ሁኔታ ማሳያ በማድረግ ተናግረዋል። ሀገራዊ ውይይቱና ድርድሩ ከተኩስ አቁም ስምምነት ባለፈ በጠረጴዛ ዙሪያ ከፖለቲካ ልሂቃን ጋር ጭምር መሆን እንዳለበት ጠቅሰዋል።

ጥምረቱ በትኩረት ሊመክርባቸው የሚገቡ አራት ዋና ዋና አጀንዳዎችን መለየቱን የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊው አስታውቀዋል። ስለ ብሔራዊ ምክክሩ ሂደት ያሉ አመለካከቶች እና ከሕጋዊ የሥራ ቋንቋ ክርክር ጋር ተያይዞ በአባላት ላይ እየደረሰ ያለው ተፅዕኖ በአጀንዳነት ተለይተዋል። በምርጫው ወቅት የታዩ የአሠራር ችግሮች እንዲሁም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድን ተግባራት ማመስገንና ተቋሙን ይበልጥ ማሻሻል ሌሎቹ ነጥቦች መሆናቸውን ገልጸዋል።

#አሐዱ_


Source: Yeneta Tube

Comments

No comments yet.

- Advertisement -
Advertisement post bottom2