የኢራን መንግሥት በሆርሙዝ የባህር ስርጥ ላይ የተጣለው እገዳ እንዲነሳና በመካሄድ ላይ ያለው ጦርነት እንዲቆም የሚያስችል አዲስ የሰላም የውሳኔ ሃሳብ ለአሜሪካ ማቅረቡ ተሰማ።
በአሁኑ ወቅት በኢራን እና በአሜሪካ መካከል ያለው ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት መረጋጋት ያጣ ሲሆን፣ የኢራን አመራሮች በኒውክሌር ጉዳይ ላይ በሚሰጡ ስምምነቶች ዙሪያ እርስ በርስ መከፋፈላቸው ይነገራል።
በመሆኑም ኢራን አሁን ያቀረበችው አዲስ ሃሳብ አወዛጋቢ የሆነውን የኒውክሌር ድርድር ለቀጣይ ጊዜ በማስተላለፍ፣ በቅድሚያ የባህር ስርጡ እንዲከፈትና የተኩስ አቁም ስምምነቱ ለረጅም ጊዜ እንዲራዘም ወይም ጦርነቱ በዘላቂነት እንዲቆም የሚያደርግ ነው።
ይህ የውሳኔ ሃሳብ በፓኪስታን አደራዳሪዎች በኩል ለዋይት ሃውስ የደረሰ ቢሆንም፣ አሜሪካ ሃሳቡን ለመቀበል ያላት ዝግጁነት ግን እስካሁን ግልጽ አልሆነም።
በሌላ በኩል ፕሬዝዳንት ትራምፕ የኢራንን የነዳጅ ኤክስፖርት አቀዝቅዞ የያዘውን የባህር ላይ እገዳ አጠናክረው ለመቀጠል ፍላጎት እንዳላቸው ፍንጭ ሰጥተዋል።
ፕሬዝዳንቱ ከፎክስ ኒውስ ጋር በነበራቸው ቆይታ፣ የባህር መንገዱ በመዘጋቱ ምክንያት የኢራን የነዳጅ ማስተላለፊያ መስመሮች ከፍተኛ ጫና ውስጥ መሆናቸውንና ይህም ቴህራንን በሳምንታት ውስጥ ለድርድር እንዲትበረከክ ያደርጋታል የሚል እምነት እንዳላቸው ገልጸዋል።
ትራምፕ ሰኞ ዕለት ከከፍተኛ የብሔራዊ ደህንነት እና የውጭ ጉዳይ ቡድናቸው ጋር በኢራን ጉዳይ ላይ በዋይት ሃውስ የሁኔታዎች መከታተያ ክፍል ውስጥ ስብሰባ እንደሚያካሂዱ ይጠበቃል።
አሜሪካ የኢራን የኒውክሌር ሃይል የማበልጸግ ሂደት ቢያንስ ለአስር ዓመታት እንዲቆምና የተከማቸው የዩራኒየም ክምችት ከሀገር እንዲወጣ የምትፈልግ ሲሆን፣ ኢራን አሁን ያቀረበችው ሃሳብ ግን እነዚህን ዋና ዋና ጉዳዮች ወደ ጎን በማለት እገዳው እንዲነሳላት የሚጠይቅ ነው።
Capital
Source: Yeneta Tube








No comments yet.