የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን ጦርነቱን ለመቋጨት ያቀረበችው አዲስ የሰላም እቅድ እንዳላስደሰታቸው ገለጹ። የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በበኩላቸው አሜሪካ አካሄዷን የምትቀይር ከሆነ ኢራን ለዲፕሎማሲ ዝግጁ መሆኗን ተናግረዋል።
የኢራን ዜና ወኪል ‘ኢርና’ ቴህራን በፓኪስታን በኩል አዲስ የድርድር እቅድ ለአሜሪካ ማቅረቧን ትናንት አስታውቆ ነበር። እቅዱ ስለያዛቸው ዝርዝር ጉዳዮች ግን በዘገባው አልተጠቀሰም።
የፓኪስታን ባለሥልጣናት በበኩላቸው የኢራንን አዲስ እቅድ ለአሜሪካ ማድረሳቸውን ገልጸዋል።
አዲስ እቅድ መቅረቡ በተሰማ በአጭር ጊዜ ውስጥ ለጋዜጠኞች አስተያየት የሰጡት ፕሬዝዳንት ትራምፕ፤ “ስምምነት ላይ መድረስ ይፈልጋሉ። እኔ አልረካሁበትም፤ ስለዚህ የሚፈጠረውን እናያለን” ማለታቸውን አሶሺዬትድ ፕሬስ ዘግቧል።
ትራምፕ ትናንት አርብ በዋይት ሐውስ ከጋዜጠኞች ጋር በነበራቸው ቆይታ በእቅዱ ውስጥ ያላስተደሰታቸው ጉዳይ ምን እንደሆነ አላብራሩም።
የኢራን አመራር “እጅጉን ተከፋፍሏል” ያሉት ፕሬዝዳንቱ፤ “ልስማማበት የማልችለውን ነገር እየጠየቁ ነው” ማለታቸውን ሮይተርስ አስነብቧል።
ትራምፕ ከቆይታ በኋላ በፍሎሪዳ ተገኝተው ንግግር ባደረጉበት ወቅትም የኢራንን ጉዳይ አንስተዋል። አሜሪካ ከኢራን ጋር የገባችበትን ግጭት በቶሎ ቋጭታ “በተጨማሪ ሦስት ዓመታት ውስጥ ችግር እንዲፈጠር” እንደማትፈቅድ ተናግረዋል።
ፕሬዝዳንት ትራምፕ ኢራን የኒውክሌር መሣሪያ እንዲኖራት እንደማይፈቅዱ በተደጋጋሚ ገልጸዋል። ኢራን ባለፈው ሳምንት ያቀረበችው የሰላም እቅድ የኒውክሌር ጉዳይ ወደ ጎን ተደርጎ የመጀመሪያው ደረጃ ድርድር ጦርነቱን መቋጨት እና ሆርሙዝን መክፈት ላይ እንዲያተኩር የሚጠይቅ ነበር።
የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ በበኩላቸው አሜሪካ የያዘችውን “የተለጠጠ አካሄድ፣ የዛቻ ንግግር እና ተንኳሽ ድርጊቶች” የምታቆም ከሆነ አገራቸው ለዲፕሎማሲ ዝግጁ መሆኗን እንደተናገሩ ሮይተርስ ዘግቧል።
ይህም ቢሆን ግን “የኢራን ጦር ኃይሎች አገሪቱን ከማንኛውም ስጋት ለመከላከል ዝግጁ መሆናቸውን” በቴሌግራም ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ ገልጸዋል።











No comments yet.