የማሊ የመከላከያ ሚኒስትር በዋና ከተማዋ ባማኮ አቅራቢያ በሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው መኪና ላይ በተጠመደ ቦምብ በተፈጸመ ጥቃት መገደላቸው ተዘገበ።
ሳዲዮ ካማራ የተገደሉት ጂሃዲስት ታጣቂዎች እና ተገንጣዮች በመላ አገሪቱ በከፈቱት የተቀናጁ የጥቃት ማዕበሎች አካል በሆነ እርምጃ መሆኑን የበርካታ የዜና አውታሮች ዘገባ አመልክቷል።
የአገሪቱ መንግስት ቴሌቪዥን ከጥቂት ሰዓታት በኋላ ሚኒስትሩ በደረሰባቸው ቁስል መገደላቸውን ዘግቧል። የወታደራዊው ጁንታ መሪ ጄኔራል አሲሚ ጎይታ ቤታቸው ዒላማ መደረጉን ተከትሎ ደኅንነቱ ወደተጠበቀ ቦታ ተዛውረዋል ተብሏል።
በማሊ ጦር የተቀጠሩት የሩሲያ ቅጥረኛ ነፍሰ ገዳዮች ከሁለት ቀናት ግጭት በኋላ ከኪዳል ለመውጣት ተስማምተዋል ሲል የተገንጣዩ የአዛዋድ ነፃ አውጪ ግንባር (ኤፍኤልኤ) ተናግሯል።
ማሊ ለዓመታት በአል ቃይዳ እንዲሁም ከእስላማዊ መንግስት (አይኤስ) እና ከኤፍኤልኤ ጋር በተያያዙ ቡድኖች ጥቃት ሲፈጸምባት ቆይታለች።
የካማራን ቤተሰብ እና የፈረንሳይ ሚዲያዎችን በመጥቀስ ከአልቃይዳ ጋር ግንኙነት ባላቸው ታጣቂዎች ቅዳሜ ዕለት ካቲ ውስጥ በተፈጸመው ጥቃት ቢያንስ ሦስት የካማራ ቤተሰብ አባላት መገደላቸውን የዜና ወኪሎች ዘግበዋል።
የመንግስት ቃል አቀባይ ኢሳ ኦስማን ኩሊባሊ እሑድ ምሽት ባነበቡት መግለጫ ካማራ “ፈንጂ የተሞላበት እና በአጥፍቶ ጠፊ በሚነዳ ተሽከርካሪ የሚኒስትሩ መኖሪያ ቤት ጥቃት በተሰነዘረበት ወቅት ተገድለዋል” ብለዋል።
ከአጥቂዎቹ ጋር የተኩስ ልውውጥ እንዳደረጉ እና “አንዳንዶቹን በማስወገድ ረገድ እንደተሳካላቸው” ተናግረዋል። ሆኖም ግን ቆስለው በሆስፒታል ከደረሱ በኋላ ህይወታቸው አልፏል።









No comments yet.