በኦርዌል “1984” እና የኢትዮጵያ ፖለቲካ ምንና ምን ናቸው?

- Advertisement -
Sidebar AD

(ቃልኪዳን ኃይሉ)
ጆርጅ ኦርዌል ማነው?

#Ethiopia | ​ጆርጅ ኦርዌል (ትክክለኛ ስሙ ኤሪክ አርተር ብሌየር) እ.ኤ.አ. በ1903 ሕንድ ውስጥ ተወለደ። ጆርጅ ኦርዌክ በሕይወቱ ለጽሑፎቹ ትልቅ ግብዓት የሆኑ ሦስት ዋና ዋና ምዕራፎች ነበሩት፦ እነሱም ​የፖሊስነት ተሞክሮ፣ በአውሮፓ የነበረው የድህነት ኑሮ እና ​የስፔን የእርስ በርስ ጦርነት፡ በፋሺዝም ላይ ለመዋጋት ወደ ስፔን ሄዶ በጦርነቱ መሳተፉ አስተሳሰቡን እና መጻሕፍቱን በዚያ ልምድና ተሞክሮው ላይ እንዲያጠነጥን አድርጎታል።

​ኦርዌል በተለይ በሁለት ዝነኛ መጻሕፍቱ ይበልጥ ይታወቃል፦​Animal Farm (የእንስሳት እርሻ) እና 1984 ነው።

Animal Farm የራሺያን አብዮት መነሻ በማድረግ የተጻፈ ተምሳሌታዊ (Allegory) ድርሰት ነው። “ሁሉም እንስሳት እኩል ናቸው፤ ነገር ግን አንዳንዶቹ ከሌሎቹ ይበልጥ እኩል ናቸው” የሚለው ዝነኛ ጥቅሱ ሥልጣን እንዴት አብዮተኞችን ወደ ጨቋኝነታቸው እንደሚቀይር ያሳያል።

ሌላው ​1984 ይህ ደግሞ የግለሰብ ነፃነት ሙሉ በሙሉ በጠፋበት ዓለም ውስጥ የሚኖርን ሰው ሕይወት የሚተነብይ የ”ዳይስቶፒያ” (Dystopia) ልብ-ወለድ ነው።

​የመከራከሪያ ነጥቦቹ (Core Ideas)
​ኦርዌል በሥራዎቹ ውስጥ ሦስት መሠረታዊ ነገሮችን በጽኑ ይቃወማል፦

1.​የእውነት መጥፋት (The Erosion of Truth)፦ ኦርዌል በጣም የሚፈራው “እውነት” የሚባል ነገር ጠፍቶ፣ ገዢዎች የሚሉትን ብቻ ሕዝቡ እንዲያምን የሚደረግበትን ሥርዓት ነው። “በሁለንተናዊ የማታለል ዘመን እውነትን መናገር አብዮታዊ ተግባር ነው” የሚል እምነት ነበረው።

2.​የቋንቋ መበላሸት (Corruption of Language)፦ ፖለቲከኞች መጥፎ ተግባራቸውን ለመሸፈን ቋንቋን እንደሚጠቀሙ ይከራከራል። ለምሳሌ “ሰላም ማስከበር” የሚለው ቃል ጦርነትን ለመሸፈን፣ “ማስተካከል” የሚለው ቃል ደግሞ ግድያን ለመሸፈን ጥቅም ላይ ሊውል እንደሚችል ያሳያል።

3. ​የግለሰብ ነፃነት (Individual Autonomy)፦ ሥልጣን የሰውን ልጅ አካል ብቻ ሳይሆን አእምሮውንና ትውስታውን ጭምር እንዲቆጣጠር ኦርዌል አይፈልግም።

“ኦርዌሊያን” (Orwellian) የሚለው ቃል
​በአሁኑ ጊዜ ይህ ቃል በዓለም አቀፍ ደረጃ እንደ ቅጽል ጥቅም ላይ ይውላል። አንድን ሁኔታ “ኦርዌሊያን” ስንለው፣ ያ ሁኔታ መንግሥት የሰዎችን የግል ሕይወት የሚቆጣጠርበት፣ መረጃን የሚያዛባበትና ዜጎችን በውሸት ፕሮፓጋንዳ የሚያደነዝዝበት መሆኑን ለመግለጽ ነው።

1984 Vs ኢትይጵያ

​”1984″ እስካሁን ድረስ ጸንቶ የቆየው እንደ ተራ የአምባገነንነት ማስጠንቀቂያ ሳይሆን፣ ሥልጣን ከተራ የተግባር ቁጥጥር ባለፈ የአረዳድ (Perception) የበላይነትን ለመያዝ በሚሻበት ጊዜ እንዴት እንደሚሠራ የሚያሳይ ጥቁር ትንታኔ በመሆኑ ነው።

በጥልቅ ሲታይ፣ ሥርዓቱ በእውቀት ቁጥጥር (Epistemic Control)፣ በቋንቋ ምህንድስና እና በሥነ-ልቦናዊ ተገዥነት ላይ የተገነባ መሆኑን እንረዳለን።

​1. ሥልጣን እንደ እውነት የማምረቻ መሣሪያ

​የኦርዌል ዋነኛ መከራከሪያ ፍጹም ፖለቲካዊ ሥልጣን የሚገኘው እውነታን የመተርጎም አቅም ላይ ነው የሚል ነው። “ፓርቲው” ነባራዊ እውነታዎች ለፖለቲካዊ ፍላጎት ተገዥ መሆን አለባቸው ብሎ መሟገቱ እንዲሁ ለንግግር ያህል የመጣ ሳይሆን መዋቅራዊ መርህ ነው። የሚጋጩ እውነታዎችን በግዴታ አምኖ መቀበል (Doublethink) ዜጎችን የማላመጃ ዘዴ ሲሆን፣ በእውነትና በሥልጣን መካከል ያለውን ድንበር ያጠፋዋል።

​በኢትዮጵያ ሁኔታ፡ አሁን በኢትዮጵያ የፖለቲካ ውድድር በዋነኝነት የሚካሄደው በትርክት ግንባታ (Narrative Construction) ነው።

የመንግሥት ተቋማት፣ የተቃዋሚ ንቅናቄዎች እና የሚዲያ ተዋናዮች ስለ ግጭት፣ ስለ ሪፎርም እና ስለ ቅቡልነት የተራራቁ ትርክቶችን ያቀርባሉ። እዚህ ላይ ችግሩ የፕሮፓጋንዳ መኖር ብቻ ሳይሆን፣ “ትክክለኛውን የታሪክ ስሪት” የማጽደቅ ፍልሚያ ነው። የጋራ የሆነ የእውነታ መሠረት በሌለበት ሁኔታ፣ ፖለቲካዊ ፍርድ በቀላሉ የሚለዋወጥና ለማጭበርበር የተጋለጠ ይሆናል።

​2. የቋንቋ ቅነሳና ፖለቲካዊ ቅርጻ (Linguistic Compression and Framing)

​”ኒውስፒክ” (Newspeak) ቋንቋ የሐሳብ መሠረት (Infrastructure) መሆኑን በሚገባ የተረዳ ስልት ነው። የቃላት ግምጃ ቤትን በዘዴ በመቀነስ፣ ፓርቲው ተቃውሞን ለማሰብ የሚያስፈልጉ የግንዛቤ መሣሪያዎችን ያጠፋል።

​በኢትዮጵያ ሁኔታ፡ ምንም እንኳ አተገባበሩ እንደ መጽሐፉ የተማከለ ባይሆንም፣ ውጤቱ ግን ተመሳሳይ ነው። ከማንነት፣ ከፌዴራሊዝም፣ ከሉዓላዊነትና ከደኅንነት ጋር የተያያዙ ቃላት በጽንፍ በተራራቁ መንገዶች ጥቅም ላይ ይውላሉ።

ትንታኔዎች በታፔላዎች (Labels) ይተካሉ። ውስብስብ የሆኑ ነባራዊ ሁኔታዎች በስሜት ወደተሞሉ ምድቦች ይጠቅለላሉ። ይህ ሐሳብን ባያጠፋውም እንኳ፣ አስቀድሞ ወደ ተወሰኑ የፖለቲካ አሰላለፎች እንዲፈስ ያደርገዋል። ውጤቱም ውይይቶች ገና ሳይጀመሩ በቋንቋ አጠቃቀም ብቻ ውጤታቸው እንዲወሰን ያደርጋል።

​3. የታሪክ ትርክትና የማስታወስ ፖለቲካ

​ፓርቲው ያለፈውን ታሪክ በመቆጣጠር፣ ከሥርዓቱ ቁጥጥር ውጭ የሆነ ነፃ የማጣቀሻ ነጥብ እንዳይኖር ያደርጋል። ታሪክ ለወቅታዊው ሥልጣን ቅቡልነት ሲባል በየጊዜው የሚስተካከል ተለዋዋጭ ነገር ይሆናል።

​በኢትዮጵያ ሁኔታ፡ በኢትዮጵያም እርስ በርሳቸው የሚጋጩ የታሪክ ትርክቶች ለወቅታዊ የፖለቲካ ጥያቄዎች ድጋፍ እንዲሆኑ ተደርገው ይቀርባሉ።

ስለ ሀገር ምስረታ፣ ስለ ማንነትና ስለ ታሪካዊ በደሎች የሚደረጉ ክርክሮች የትምህርት ዘርፍ ብቻ ሳይሆኑ የፖለቲካ መሣሪያዎች ናቸው። በታሪክ ትርጓሜ ላይ ስምምነት አለመኖሩ፣ ለጋራ ሀገራዊ ትርክት መፈጠር እንቅፋት ከመሆኑም በላይ ተጠያቂነትንና እርቅን የማምጣት ሂደትን ያወሳስበዋል።

​4. ቁጥጥር፣ ራስን መገደብና የሕዝብ ውይይት

​”ቴሌስክሪን” (Telescreen) የማያቋርጥ ክትትልን ያመለክታል፤ ሆኖም ዋናው ተግባሩ ግለሰቡ “እየታየሁ ነው” የሚለውን ስሜት ውስጣዊ አድርጎ ራሱን እንዲቆጣጠር ማድረግ ነው።

​በኢትዮጵያ ሁኔታ፡ ክትትል በተቋማዊ፣ በዲጂታልና በማኅበራዊ መዋቅሮች አማካኝነት ይከናወናል። ምንም እንኳ ቁጥጥሩ ፍጹም ባይሆንም፣ ዜጎች የሚናገሩትን ነገር እንዲመጥኑ (Calibrate) እና ራሳዊ ቅድም ምርመራ (Self censorship) ያደርጋል።

የማኅበረሰብ አንቂዎች፣ ጋዜጠኞች፣ ተንታኞችና ተራ ዜጎች በሕግ፣ በፖለቲካዊ ተጋላጭነትና በማኅበራዊ ጫናዎች የሚወሰኑ ድንበሮችን እያጤኑ ይንቀሳቀሳሉ
(Self censorship)። ውጤቱም ፍጹም ዝምታ ሳይሆን፣ ያልተባለው ነገር ከተባለው እኩል ትርጉም የሚሰጥበት “ስልታዊ የሐሳብ ልውውጥ” (Strategic Communication) መፈጠሩ ነው።

​5. ማስገደድና የውዴታ ግዴታን ማምረት (Coercion and Consent)

​በመጽሐፉ ውስጥ የሚገኘው የኦብራይን (O’Brien) ገጸ-ባህሪ ዓላማው ተቃውሞን ማጥፋት ብቻ ሳይሆን፣ የሰውን እምነትና አስተሳሰብ ጭምር እንደ አዲስ መቅረጽ ነው።

​በኢትዮጵያ ሁኔታ፡ የፖለቲካው ምኅዳር የተለያየና ብዙ ተዋናዮች የሚሳተፉበት በመሆኑ፣ ጫናው እንደ ኦርዌል ዓለም ወጥና ፍጹም አይደለም። ይሁን እንጂ የሕዝብን ድጋፍ በትርክት የማምረት ፍላጎት ማዕከላዊ ነው። የሚዲያ ሥነ-ምህዳሩ (መደበኛም ሆነ ማኅበራዊ) የተወሰኑ ትርክቶችን በማግነንና ሌሎችን በማዳከም ረገድ ትልቅ ሚና ይጫወታሉ።

ትግሉ አንድ ወጥ የሆነ አስተሳሰብን ከመጫን ይልቅ፣ በተሰባበረ የመረጃ አውድ ውስጥ የትርክት የበላይነትን (Narrative Dominance) የመያዝ ትግል ነው።

​ማጠቃለያ
​የ”1984″ ፋይዳ ያለው በፅንሰ-ሐሳብ ግልጽነቱ ላይ ነው። ሥልጣን ግንዛቤን፣ ቋንቋንና ትውስታን በመቆጣጠር ራሱን እንዴት እንደሚያደላድል ነጥሎ ያሳየናል።

​ኢትዮጵያ የኦርዌልን ዝግ የአምባገነንነት፣ የፖለቲካው ሜዳ ተለዋዋጭና የተለያየ ተፅዕኖ ያላቸው ኃይሎች የሚጋጩበት ነው።

ኦርዌል የለያቸው መሠረታዊ መዋቅሮች መልክ ቀይረው ይታያሉ። መረጃን መቆጣጠር፣ ቋንቋን ለፖለቲካ ዓላማ መጠቀምና ታሪክን ፖለቲካዊ ማድረግ እስካሁንም የሥልጣን ትግሉ ማዕከል ናቸው።





Source: GetuTemesgen

Comments

No comments yet.

- Advertisement -
Advertisement post bottom2

You might want to listen to: