በጎንደር ነፃ የሕፃናት ልብ ቀዶ ሕክምና ዘመቻ ተጀመረ

- Advertisement -
Sidebar AD

#FastMereja በከባድ የልብ ሕመም ለሚሰቃዩ ሕፃናት ተስፋና ፈውስን ይዞ የመጣውና ለሦስት ቀናት የሚቆየው የነፃ የሕፃናት ልብ ቀዶ ሕክምና ዘመቻ በጎንደር ዩኒቨርሲቲ አጠቃላይ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ዛሬ በይፋ መካሄድ ጀምሯል። ለዚህ ታላቅ ሰብአዊ ተልዕኮ ወደ ስፍራው ለገሰገሰው ዓለም አቀፍ የሕክምና ቡድን ዛሬ ጠዋት ደማቅ የአቀባበል ሥነ-ሥርዓት የተደረገለት ሲሆን፣ ቡድኑም ወዲያውኑ ሥራውን በይፋ አስጀምሯል። ይህ ሕይወት አታራፊ ተነሳሽነት ሊሳካ የቻለው በHeart to Heart Children’s Aid፣ በኢትዮ-ኢስታንቡል አጠቃላይ ሆስፒታል፣ በፓድሬ ፒዮ ኢጣሊያ፣ በኢፌድሪ ጤና ሚኒስቴር እና በጎንደር ዩኒቨርሲቲ መካከል በተደረገ ጠንካራ ትብብር ሲሆን፣ በኢትዮጵያ ለሚገኙ ተጋላጭ ሕፃናት ልዩ የሕክምና አገልግሎትን ተደራሽ ለማድረግ የተፈጠረውን የጋራ ቁርጠኝነት በተግባር የሚያሳይ ነው።

በዛሬው ዕለት ሥራቸውን በይፋ የጀመሩት ከፍተኛ ልምድ ያላቸው ዓለም አቀፍ የልብ ቀዶ ሕክምና ስፔሻሊስቶችና የሕክምና ባለሙያዎች፣ የላቀ የሕፃናት ልብ ቀዶ ሕክምናና ልዩ የልብ ሕክምና አገልግሎቶችን ለሕጻናቱ ሙሉ በሙሉ በነፃ መስጠት ጀምረዋል። በዚህ ወሳኝ የሕክምና ጣልቃ ገብነት ወደ 20 የሚጠጉ ሕፃናት ቀጥተኛ ተጠቃሚ ይሆናሉ ተብሎ ይጠበቃል። ይህ ዘመቻ በአሁኑ ወቅት ሕጻናቱን በነፃ ከማከም ባለፈ፣ ወደፊት አገሪቱ በዘርፉ ራሷን እንድትችል በዓለም አቀፍ ባለሙያዎችና በአገር ውስጥ የጤና ባለሙያዎች መካከል የእውቀትና የባለሙያ ልምድ ልውውጥ ለማድረግ ዛሬውኑ ትልቅ ዕድልና መሠረት እየጣለ ይገኛል።

የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር አሥራት አጸደወይን ዛሬ በነበረው የአቀባበል መርሐ-ግብር ላይ ዓለም አቀፉን የሕክምና ቡድን ከፍተኛ አክብሮት ባለው ስሜት እንኳን ደህና መጣችሁ በማለት የተቀበሉ ሲሆን፥ ለሁሉም አጋር ድርጅቶች ስላሳዩት ሰብአዊነትና ፈጣን ድጋፍ ልባዊ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።

ፕሬዝዳንቱ አክለውም ይህ ተነሳሽነት የዓለም አቀፍ አጋርነት፣ የርኅራኄ እና የሕክምና አንድነት ትልቅ ማሳያ ከመሆኑም በላይ፣ ወደፊት በኢትዮጵያ የረጅም ጊዜ የሕፃናት ልብ ሕክምና አገልግሎትን በዘላቂነት ለመገንባትና ለማሳደግ ጉልህ አስተዋፅኦ ያበረክታል ብለዋል። በተጨማሪም ዘመቻው የሕፃናትን ሕይወት ከመታደግ ባለፈ ለቤተሰቦቻቸው ተስፋን የሚመልስና የሕፃናትን ጤናና የወደፊት ሕይወት ለመጠበቅ ያለንን የጋራ ቁርጠኝነት የሚያጠናክር መሆኑን ገልጸዋል::






Source: FastMereja

Comments

No comments yet.

- Advertisement -
Advertisement post bottom2

You might want to listen to: