የመድፈኞቹ የሊግ ዋንጫ ድርቅ ማክተምና የለንደን የበላይነት ማረጋገጫ

- Advertisement -
Sidebar AD

#Ethiopia | የሰሜን ለንደኑ ክለብ አርሰናል ለ22 አመታት ያህል የዘለቀውን የፕሪሚየር ሊግ ዋንጫ የማጣት መርገምት በመስበር የለንደንን ቀይነት በይፋ አውጇል፡፡

ይህ ከታሪካዊው የ2003-04 ያለመሸነፍ ጉዞ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ የተመዘገበ የሻምፒዮንነት ድል ሲሆን ረጅሙን የናፍቆት ዘመንም አብቅቷል፡

ይህ ድል የመጣው በጠንካራ ስፖርታዊ ጽናት እና ጥረቶች ነው፡፡ እንደ አለት የጠነከረው የተከላካይ ክፍል፣ የግብ ጠባቂው ዳቪድ ራያ አስደናቂ አድናቆቶች፣ የኒኮላ ጆቨር ድንቅ የቆሙ ኳሶች አጠቃቀም ስልት እና የቡድኑ ጠንካራ ውህደት ለአሰልጣኝ ሚኬል አርቴታ ስኬት ቁልፍ ምክንያቶች ነበሩ፡፡

መድፈኞቹ ባለፉት ሶስት የውድድር አመታት ሁለተኛ ደረጃን ይዘው ካጠናቀቁ በኋላ በተለይም ዋንጫው በሁለት ነጥብ ብቻ በጠፋበት የ2023-24 የውድድር ዘመን የደረሰባቸውን የስነ ልቦና ጠባሳ ተቋቁመው ማለፍ ችለዋል፡፡

ከቀድሞው ማራኪ ግን መጨረሻ ላይ በግፊት ከሚፈራርሰው አጨዋወት በተለየ የ2025-26ቱ ስብስብ ሙሉ በሙሉ በቁርጠኝነት እና በውጤታማነት ላይ የተገነባ ነበር፡፡

የሳን ሴባስቲያኑ ተወላጅ ሚኬል አርቴታ ተስፋ መቁረጥና ቸልተኝነት የነገሰበትን የመልበሻ ክፍል እና የቀዘቀዘውን የስታዲየም ድባብ ወደ አስፈሪና ተፎካካሪ ቡድን ለመቀየር ስድስት አመታትን ፈጅቶበታል፡፡

በዚህ የውድድር ዘመን የአርቴታ ታክቲክ በአንድ ተጫዋች ላይ ብቻ ያልተመሰረተ ሲሆን የጎል ማግባት ኃላፊነቱ በሁሉም ላይ የተከፋፈለ ነበር፡፡

በክረምቱ ክለቡን የተቀላቀለው ስዊድናዊው ቪክቶር ጊዮከሬሽ 14 ጎሎችን ቢያስቆጥርም ቡካዮ ሳካ፣ ኤቤሬቺ ኢዜ፣ ሊያንድሮ ትሮሳርድ እና በርንሌይ ላይ ወሳኝ ጎል ያስቆጠረው ካይሀቨርትዝ ለቡድኑ ማጥቃት ትልቅ አስተዋጽኦ አበርክተዋል፡፡

በዚህ ስኬት ሚኬል አርቴታ ለተጫወተበት ክለብ በአሰልጣኝነት ዋንጫ በማንሳት የመጀመሪያው ሰው መሆን ችሏል፡፡

እ.ኤ.አ. በታህሳስ 2019 ቡድኑን ከተረከበበት ጊዜ ጀምሮ የአሸናፊነት ባህልን በመገንባት፣ በትችቶች ውስጥ በመጽናት እና ጠንካራውን ማንቸስተር ሲቲን በመብለጥ ታሪክ ሰርቷል፡፡

የውድድር ዓመቱ ማብቂያ በሰልኸርስት ፓርክ ከክሪስታል ፓላስ ጋር የሚደረገው ጨዋታ የክብር ጉዞ ቢሆንም የአርሰናል ጉዞ ግን ገና አልተጠናቀቀም፡፡

የሀገር ውስጥ ውድድር ቢጠናቀቅም ከፊት ለፊታቸው ትልቅ የአውሮፓ መድረክ ይጠብቃቸዋል፡፡

ግንቦት 22 ቀን 2018 ዓ.ም የእንግሊዝ ሻምፒዮኖቹ መድፈኞች በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ፍፃሜ የፈረንሳዩን ኃያል ፓሪስ ሴንት ዠርሜንን ለመግጠም ወደ ቡዳፔስት ሀንጋሪ ያመራሉ፡፡

ያንን ጨዋታ ካሸነፉ የአርቴታ ስብስብ በታሪክ አናት ላይ ብቻቸውን የሚቀመጡበት ታላቅ የውድድር ዘመን ይሆናል፡፡

ጋዜጠኛ ብሩክ ተስፋዬ

#arsenal #premierleague #mikelarteta #football #champions #getutemesgen #getu #ጌጡ #ጌጡተመስገን #addisababa



Source: GetuTemesgen

Comments

No comments yet.

- Advertisement -
Advertisement post bottom1