( የአልፎ ሂያጁ ማስታወሻ )
ቴዎድሮስ ተ/አረጋይ
#በመጨረሻም ፦ ጽሑፉ ለፌስቡክ ረጅም ( አረፍ አረፍ እየተባለ ተነቦ የሚያልቅ ) ነው ። አጥሮ ሁሉም ጋ ከሚደርስ ረዝሞ የሚመለከታቸውና የሚያስፈልጋቸው ቢያነቡት መርጬ ነው ። ሆነ ብዬ ነው ማለት ነው ። ይሁን ። እንግዲህ እያረፋችሁም ፣ እያለፋችሁም አንብቡት ።
ለግጥምም ፣ ለዜማም አልፎ ሂያጅ ነኝ። ( በተለይ ) ለግጥም አልፎ ሂያጅ መሆኔ ያስቆጨኛል ። ግጥም ምኞቴ ነው ፤ ጉድለቴም ። ማንም እንደሚሰማውና እንደሚረዳው ነኝ ። አዚያዚያምን መረዳትም ላይ ጨዋ አላዋቂ ነኝ ። ቤተልሔም ሸረፈዲን ” ደስተኛ ” ብላ ስለሰየመችው አዲሱ አልበሟ የተሰማኝን ልላችሁ ነው ዳር ዳር የምለው ።
እኔ የምለው ፣ ቤተልሔም ሸረፈዲን ግን ስንት ዓመቷ ነው ? በቅርቡ ትንሽ ልጅ አልነበረችም እንዴ ? ከመቼው አደገች ? ከምኔው አብባ አፈራች ? አልበሟ በተለቀቀበት ” ኩራ ስትሪም ” ላይ ገጣሚው ናትናኤል ግርማቸው ( ናቲ ) እንደ ገጣሚነቱ ቃላት ቆጥቦና ሀሳቡን አስውቦ ” የልጅ ልብና የአዋቂ ጆሮ አላት ” እንዳላት ሆና ነው የመጣችው ። የጥበብ ስራ አመዛኙን ሁለቱን ይፈልጋል ። እውቀትም ፣ ተሰጥዖም በዝቶ ኖሯቸው የትም ሳይደርሱ የቀሩ ” እገሌ ፣ እገሌ ” የምንላቸው ጥቂት የማይባሉ የጥበብ ሰዎች በየአልባሌው ወድቀው ቀርተዋል ። እስቲ እነዚህን ሰዎች አስቧቸው ። የህጻን ልብም ፣ የአዋቂ ጆሮም አታገኙባቸውም ።
10 ዘፈኖች የያዘው ” ደስተኛ ” አልበም ናትናኤል ግርማቸውና ታምሩ አማረ በጥምረት ፕሮዲዩስ ያደረጉት ነው ። ከጀርባቸው ደግሞ ከብዙ ጥበባትና የጥበብ ሰዎች ጀርባ ያለው ዘላለም ኩራባቸው ” ኩራ ስትሪም ” ን ይዞ አለ ። ቅንብሩን ፣ ሚክሲንግ እና አሬንጅመንቱን ታምሩ አማረ ፣ ግጥሞቹን ( በሙሉ ) ናትናኤል ግርማቸው ( ናቲ ) ፣ ” ባለቤቴ ” እና ” እንዴት ” ዜማዎችን ዮሴፍ በቀለ ( ጆ ) ፣ ” አይታለፍም ” ዜማ እሱባለው ይታየው ( የሺ ) ፣ የቀሪዎቹን 7 ስራዎች ዜማዎች በምህረተአብ ደስታ ሲፈጠሩ ከእነዚህ ውስጥ የእበሙ መጠሪያ የሆነው ” ደስተኛ ” ን ዜማ ናቲና ምህረተአብ በጋራ ሰርተዋቸዋል ።
በአሁኑ ጊዜ አንድ ነጠላ ዜማ መስራት የምረቃ ፕሮግራም ያዘጋጃል ፤ ወዳጅ ዘመድ ያጠራራል ፤ ” ሰይፉ በኢቢኤስ ” ላይ ያስቀርባል ፤ ማህበራዊ ሚዲያው ላይ አላስቆም አላስቀምጥ ያስብላል ። አልበም መስራት ( አድማጭ ያልተቀበለውም ቢሆን እንኳ ) እንደ አራሷ ሴት ” ምጡን ተዪው ፤ ልጁን እዪው ” እየተባለና የስቃዩ ጊዜ እየተረሳ እንጂ ደጋግሞ በስሜት ሞቶ መነሳት ነው ። የሚያገጫጭ ፣ የሚያነጫንጭ ፣ የሚያቀያይምንና ” ሁለተኛ ብንገናኝ ! ” የሚያባብል ነው ። የምጡ ጊዜ አልፎ ልጁ ሲታይ እየተረሳ ነው አንዱ ሙዚቀኛ ከሌላው ጋር የኖረው ። ቤተልሔም መልካሞችና ህልም ያላቸው ሙያተኞች እጅ ላይ አሳርፏት እንጂ ጀምሮ አለመጨረስ ፣ ወድቆ አለመነሳትም አለ ። ገና በመጀመሪያው አልበም ፣ በትንሽ እድሜ ፣ በጀማሪነት አረዳድ እንዲህ ያለ ስኬታማ አልበም መስራት ደጋግሞ የማያጋጥም ነው ። ህብስት ጥሩነህ እነ አየለ ማሞ ( ማንዶሊን ) እና ታንጎ ሙዚቃ ቤትን እንዳገኘችው አይነት እድለኛነት ይጠይቃል ። የናቲ እና ታምሩ ጥምረት ደግሞ የእነ ኤሌክራትን እና አምባሰልን ዘመን ያስታውሰናል ።
ናቲ ” ኩራ ስትሪም ” ላይ 4 ዓመት ስላለፈው ” ደስተኛ ” አልበም ሲናገር ” አልበሙን ጀምረነው ባልነው ጊዜ ያልጨረስነው እኛ በዚያ ውስጥ እየተሰራን ስለነበረ ነው ” ይለዋል ። ፕሮዲዩሰሮቹ በምን በምን እንደተሰሩ አላውቅም ። ቤተልሔምን ግን በእርግጥም ሰርተዋታል ። አፈሩን ቆፍረውና አልመው ፣ አቡክተው ቤተልሔምን እንደ ውቡ ሸክላ አስጊጠው ሰርተዋታል ። እሷ እንደምትለውም ትንሿ ቤተልሔም ” ከብዙ ልምምድ በኋላ የመጣ አልበም ” ባለቤት እንትሆን አድርገዋታል ። ቤተልሔም ሸረፈዲን የተባለች ጥንቅቅ ፣ ጥፍጥ ያለ ስራ ያላት ድምጻዊትን ለዘመኑ የሙዚቃ ኢንዱስትሪ ( ? ) አበርክተዋል ። አሁን የኢትዮጵያ ዘመናዊ ሙዚቃ ቤተልሔም ሸረፈዲን የምትባል ብስል ፣ ትክን ያለች ድምጻዊት አለችለት ። ቤተልሔም ስለ አዲሱ አልበሟ ለኩራ ስትሪም ስትናገር ” ይሄን አልበም እንደ መጀመሪያም ፣ እንደ መጨረሻም ስራ አድርጌ ነው የማየው ። ” ብላለች ።
ናትናኤል ግርማቸው ገጣሚነት ተሰጥቶታል ። ገጣሚነቱ የቃላት ድርደራ ሳይሆን የሀሳብ ስፋት የታደለው ነው ። ናቲን በራሄል ጌቱ ” ኢትዮጵያዬ ” ነው ያወቅኩት ። የራሷን የራሄል ጌቱን ” ያገሬ ሰው ” ፣ በኋላም ” ወረት ” ን ሰርቶ አስደንቆኛል ። ናቲን በራሄል ጌቱ ( በስራዎቿ ) በኩል ነው ያገኘሁት ። ይህ ሰው ነው ደግሞ ከታምሩ አማረ ጋር ሆኖ ቤተልሔም ሸረፈዲንን ያገኛት ። ሁለቱ በፕሮዲዩሰርነት ባይከሰቱ ቤተልሔም ሸረፈዲን ቢያንስ በዚህ ጊዜ አትወለድም ። የጀርባ አቅሟን ባላውቅም የ10 ግጥም ፣ የ10 ዜማ ፣ የ10 ዜማዎች ቅንብር ፣ ሚክሲንግ እና ማስተሪንግ ክፍያን አትወጣውም ( ብዬ እገምታለሁ ) ። ከሁሉም በላይ ደግሞ ዘላለም ኩራባቸውን አታገኘውም ። ዘላለም ኩራባቸው ወደ ሙዚቃ ማምረት ስራ ሲገባ ከገንዘብ የነፍስ ጥሪ ትርፉን አስቦ እንደሚሆን አምናለሁ ። ካሁን ቀደም በተናጠል ሲያደርግ የነበረውን ሙያውንና ሙያተኛውን እንደ ታላቅ ወንድም አጋር የመሆን ዝንባሌውን ተቋማዊ ቅርጽ ሰጥቶት መምጣቱ ይመስለኛል ። ቤተልሔም እድለኛ ናት ። እነ ንዋይ ደበበ ፣ ሀመልማል አባተ ፣ ጸሐዬ ዮሀንስ እና ዘመንኞቻቸው በመጡበት መንገድ ነው የመጣችው ። ሌላም እድለኛነት ( ከችሎታ ጋር ) አላት ።እነ ጠረፍ ካሳሁን ፣ ራሄል ጌቱ ፣ ለምለም ኃ/ሚካኤል ፣ ዘቢባ ግርማ ተሰርተው የወጡበት ” የኛ ” ፕሮጀክት ፣ የእነ አይዳ አሸናፊ እጅም አርፎባታል ።
ከአስሩ የ ” ደስተኛ ” አልበም ስራዎች በተሸከመው ሀሳብ ( ለእኔ ) ” ባለቤቴ ” ን የሚያህልልኝ አላገኘሁም ። ለዚህ ዘፈን ከ ” ባለቤቴ ” ይልቅ ” አትክልተኛው ” ስምም ሆኖልኛል ። ምናልባት ግን ” አትክልተኛው ” ለዘፈን ርዕስነት ያንስ ( አይሆን ) እንደሆን አላውቅም ። ሙሉ ዘፈኑን ስንሰማው ገጸባሕሪዋ በምናቧ ከዋለለችለት የምናብ ባለቤቷ ይልቅ የሰው ያልሆነ ፣ ለሰው አዕምሮ ” ሞኝ ” የሚባል ፣ ለፍጽምና የቀረበ በዝናብም ፣ በጸሐይም ስራውን የማያስተጓጉል ፣ ብርሀን መርጦ የማይመጣ ፣ በጭለማ የማይሸሸግ ፣ የማግኘትም ፣ የማጣትም ጊዜ ወዳጅ ፣ እንደ አምላክ ያለ ብርቱ ሰው ነው ። ባለቤትነቱ ህልም ሲሆን ብርቱ አትክልተኝነቱ ግን እውን ነው ። ይህ ሰው ትትርናውና ቸርነቱ እንደ አምላክ ያለ ነው ። ከማንም ፣ ከምንም የማይጠብቅ ። መስጠት ብቻ የሆነ ። በአበቦቹ መሐል ብቻ አይደለም ያለው ። ልብ ባለበት ሁሉ ነው ።
Source: GetuTemesgen








No comments yet.