በ1970ዎቹ አጋማሽ በከፍተኛ 23 ቀበሌ 09 የእግር ኳስ ቡድን ውስጥ በአንድነት ሲጫወቱ የነበሩ አብሮ አደጎች በህይወት የሌሉ የቡድን አባላትን ለመዘከርና የቀድሞ ፍቅራቸውን ለማደስ ያለመ ልዩ ስፖርታዊ መርሃ ግብር አካሄዱ።
ይህ መርሃ ግብር በዋናነት ያለፉ የቡድን አባላትን ስም ለማክበር የተዘጋጀ ሲሆን በዕለቱም አቶ ጌታቸው ወርቄ (የቡድን መሪ) እና አስር አለቃ በቀለ እሽቴ (ወጌሻ) እንዲሁም ደጀን ሀጎስ፣ እስጢፋኖስ ሀብቴ፣ ልዕል ገብረህይወት፣ ግርማ መገርሳ፣ ወንድሙ አንጌቻ፣ ሰለሞን አባተ፣ አበበ ዘውዴ እና ሰመረ ደበሳይ በክብር ታስበዋል።
በዕለቱ በተካሄደው የዕውቅና መርሃ ግብር በህይወት የሌሉ ስፖርተኞች በቤተሰቦቻቸው ተወክለው ተገቢው ክብር እንዲሰጣቸው ተደርጓል።
የዝግጅቱ አስተባባሪዎች እንደገለጹት መርሃ ግብሩ ያለፈውን ታሪክ ከመዘከር ባለፈ የወደፊት ማህበራዊ ራዕይ አለው። ይህም አሁን በሕይወት ያሉ የቡድኑ አባላትንና የቀበሌውን ነዋሪዎች በጋራ ለማገዝ እና ለማጠናከር ታስቦ እየተቋቋመ ለሚገኘው የቀበሌ 09 ነዋሪዎች ህብረት እንደ መነሻ እንዲያገለግል ታስቦ የተዘጋጀ ነው።
ለአዲሱ ትውልድ ስፖርታዊ መነቃቃትን ለመፍጠር ከነባሩ ቡድን ለቄራ 09 የጤና ስፖርት ቡድን የ20 ማልያና ቁምጣ እንዲሁም የእግር ኳስ ስጦታ ተበርክቷል።
መርሃ ግብሩ በታላቅ ድምቀት የተጠናቀቀው በነባር ተጫዋቾች እና በጤና ቡድኑ መካከል በተደረገ ጨዋታ ሲሆን፣ መደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ 3 ለ 3 በሆነ ውጤት ተጠናቆ በመለያ ምት የቀድሞው ከፍተኛ 23 ቀበሌ 09 ቡድን አሸንፎ ዋንጫውን አንስቷል።



Source: Yeneta Tube









No comments yet.