#FastMereja I ሳውድ አረቢያ ውስጥ ቢያንስ 65 ኢትዮጵያውያን ከአደንዛዥ ዕጽ ጋር በተገናኘ ወንጀል የሞት ቅጣት እንደሚያሰጋቸው ዓለም አቀፉ የሰብአዊ መብቶች ተቆርቋሪ ተቋም ሂውማን ራይትስ ዎች ዐሳወቀ። የሳዑዲ ባለሥልጣናት እስከ ባለፈው ማክሰኞ (ሚያዝያ 13 ቀን፣ 2018 ዓ.ም) ድረስ ሌሎች ሦስት ሰዎችን በስቅላት መቅጣታቸውንም ዛሬ የወጣው ተቋሙ መግለጫ ያመለክታል።
በሂውማን ራይትስ ዎች የስደተኞች እና የፍልሰተኞች መብት ከፍተኛ ተመራማሪ ናዲያ ሐርድማን፦ «ሳውድ አረቢያ በመሠረታዊ የፍርድ ሂደት የመታደም መብት በመንፈግ የኃይል ጥቃት ላልቀላቀለ ወንጀል በሞት ለመቅጣት መዘጋጀቷ ለፍልሰተኞች መብት እና ሕይወት ክብር ያለመስጠትን ያንጸባርቃል» ብለዋል።
ባለሙያዋ የሳውድ አረቢያ አጋሮች «ጊዜው ከማለፉ በፊት» በአፋጣኝ ጣልቃ እንዲገቡም ጠይቀዋል። ሂውማን ራይትስ ዎች ሳውድ አረቢያ አሲር ግዛት በሚገኘው ካሚስ ሙሻይት እስር ቤት ስለሚገኙት ሦስት ታሳሪዎች መረጃ ያላቸውን ሦስት ሰዎች ስለጉዳዩ መጠየቁን አመልክቷል።
ሦስቱም እስረኞች በቅርቡ ሰሜን ኢትዮጵያ ትግራይ ክልል ጦርነት በነበረበት ወቅት የተሰደዱ መሆናቸውን ገልጿል። የሰብአዊ መብት ይዞታይ አደገኛ በነበረበት በዚያን ወቅት በአስቸጋሪው የስደት መስመር በየመን በኩል ወደ ሳውዲ የገቡ መሆናቸውንም አመልክቷል። ገንዘብ ለማግኘትም ከየመን ወደ ሳውዲ ጫት መውሰዳቻውንም ከመረጃ ሰጪዎቹ ተረድቷል።
ሆኖም ሳውዲ ውስጥ ጫት በወንጀል እንደሚያስጠይቅ እንደማያውቁም ጠቅሷል። ከታሠሩ አንስቶ በአግባቡ ፍርድ ቤት እንዳልቀረቡ፤ በቀረቡበት አጋጣሚም አስተርጓሚ እንዳልነበራቸውና የተላለፈባቸውን ፍርድ ምንነት እንዳልተረዱም ዘርዝሯል።
ሆኖም በፀጥታ ኃይሎች መደብደባቸውና ምንነቱን ያልተረዱት ሰነድ ላይ እንዲፈረሙ መገደዳቸውንም አስታውቋል። ሂውማን ራይትስ ዎች የሚመለከታቸው መንግሥታት ሳውድ አረቢያ የሞት ቅጣቱን እንድታነሳ ግፊት እንዲያደርጉም አሳስቧል።
ዘገባው የዶይቼ ቬለ ነው
Source: FastMereja









No comments yet.