በአዲስ አበባ ከተማ ወተትን ጨምሮ የባልትና ውጤቶችን ከበዓድ ነገሮች ጋር የመቀላቀል ተግባር በስፋት እየተስተዋለ ይገኛል ተባለ
#Ethiopia | በአዲስ አበባ ከተማ ወተት ፣ ማር ፣ ቅቤን ጨምሮ ሌሎች የባልትና ውጤቶችን ከበዓድ ነገሮች ጋር የመቀላቀል ድርጊት በስፋት እንደሚስተዋል የአዲስ አበባ ከተማ ምግብና መድኃኒት ባለስልጣን አስታውቋል።ከብስራት ሬዲዮ ጋር ቆይታ ያደረጉት በባለስልጣኑ የምግብና ጤና ነክ ቁጥጥር ዳይሬክቶሬት አቶ እስጢፋኖስ ጌታቸው እንደገለፁት የምግብ ክለሳ የምግብን ጥራትና ደህንነት ወይም ንጥረ ይዘት የሚያሳንስ ህገወጥ ድርጊት ነው።
ይህም ለትርፍ ሲባል ውሃ፣ ኬሚካል እና ሌሎች ያልተፈቀዱ ንጥረ ነገሮችን ወደ ምግብ በመጨመር የምግብን ተፈጥሯዊ ይዘት መለወጥ መሆኑን አስረድተዋል ።ይህ አይነቱ ተግባር የምግብ መመረዝን፣ የሆድና የአንጀት ሕመሞችን፣ የጉበትና የኩላሊት ጉዳት እንዲሁም የረጅም ጊዜ የጤና ችግሮችን ሊያስከትል እንደሚችል ተጠቁሟል ።
ባለስልጣኑ ይህን ችግር ለመቆጣጠር መደበኛ ፍተሻ፣ የላብራቶሪ ምርመራ እና የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎችን እየሰራ እንደሚገኝ አቶ እስጢፋኖስ ገልፀው በህግ ላይ የተመሰረቱ የክትትል እርምጃዎችን እያከናወነ እንደሚገኝ ጨምረው ለጣቢያችን ተናግረዋል ።
በተጨማሪም በህገወጥ የምግብ ክለሳ ተግባር ላይ የተሰማሩ አካላት ሲገኙ ምርቶቻቸውን የማስወገድ ፣ የንግድ ፈቃዳቸውን የማገድና የመሰረዝ እንዲሁም ሌሎች ህጋዊ እርምጃዎች እንደሚወሰድባቸው ባለስልጣኑ አስታውቋል።
Getu Temesgen – (ጌጡ ተመስገን)
#getutemesgen #getu
Source: GetuTemesgen









No comments yet.