#FastMereja I የኢፌዲሪ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን በደረቅ ቆሻሻ አያያዝ እና አወጋገድ አዋጅ ቁጥር 1383/2017 መሰረት፣ የማሸጊያ ፕላስቲኮችን ያለአግባብ ለንግድ ዓላማ የሚያውሉ ተቋማት እና ግለሰቦች ላይ ህጋዊ እርምጃ መውሰድ መጀመሩን አስታውቋል።
በአዋጁ መሰረት “የማሸጊያ ፕላስቲክ” ተብሎ የተገለጸው ዕቃዎችን ከብክለት ለመከላከል ወይም ከሌላ ነገር ጋር እንዳይቀላቀል ለማድረግ በአምራቾች ብቻ ጥቅም ላይ የሚውል መጠቅለያ ነው። ይሁን እንጂ፣ በአሁኑ ወቅት በአንዳንድ የችርቻሮ ሱቆች፣ ሱፐር ማርኬቶች፣ ዳቦ ቤቶች እና ሌሎች ንግድ ተቋማት ይህንን የፕላስቲክ አይነት እንደ ፌስታል (የፕላስቲክ ከረጢት) ምትክ እየተጠቀሙ እንደሚገኙ በመስክ ምልከታ ተረጋግጧል።
ይህ ተግባር በህግ ከተደነገገው ዓላማ ውጪ በመሆኑ፣ ማንኛውም ተቋም ወይም ግለሰብ ከዚህ ድርጊት እንዲቆጠብ ባለስልጣኑ በጥብቅ አሳስቧል።
መመሪያውን በመተላለፍ የማሸጊያ ፕላስቲኮችን በህገ-ወጥ መንገድ የፌስታል ተኪ አድርጎ የሚጠቀም አካል ላይ በአዋጁ መሰረት አስተዳደራዊ እና ህጋዊ እርምጃዎች እየተወሰደ እንደሚገኝ እና ይህ ቁጥጥር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተገልጿል።
Source: FastMereja









No comments yet.