#Ethiopia | የደቡብ አፍሪካ ፀረ-ስደተኛ ቡድኖች ህገ-ወጥ የተባሉ የውጭ ሀገር ዜጎች ከደቡብ አፍሪካ ለቀው እንዲወጡ ያስቀመጡት የሰኔ 30 /ሰኔ 23 የጊዜ ገደብ ማብቃቱን ተከትሎ በተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች ከፍተኛ ውጥረት ነግሷል።
የተቃውሞ ሰልፉ ወደ ከፋ ሁከትና ብጥብጥ ያመራል የሚለው ስጋት በሰፊው በማንዣበቡ ፣ በሀገሪቱ ያሉ ሰራተኞች ወደ ስራ ከመሄድ ተቆጥበዋል ፣ የንግድ ሱቆች ተዘግተዋል ፣ እንዲሁም የሕዝብ ትራንስፖርት አገልግሎቶች ተቋርጠዋል።
በደርባን እና በጆሃንስበርግ መሃል የሚገኙ አብዛኞቹ ሱቆች እና የንግድ ተቋማት የዝርፊያ ስጋት ስላለባቸው ተዘግተዋል።
ሰራተኞችና ጉዳይ ያለባቸው ተጓዦችም በቤታቸው ለመቆየት መርጠዋል።
በደርባን ከተማ የዙሉ ባህላዊ አልባሳትን የለበሱ፣ ዱላ እና ጋሻ የያዙ አነስተኛ የሰልፈኞች ቡድኖች በአንድ ፓርክ ውስጥ ተሰብስበው „አባሀምቤ“ (ይሂዱ/ልቀቁ) የሚሉ መፈክሮችን እያዜሙ ይገኛሉ።
የደቡብ አፍሪካ የፀጥታ ኃይሎች ሰልፈኞቹን በቅርብ እየተከታተሉ ነው።
ይህ የጊዜ ገደብ ካለፉት ሳምንታት ጀምሮ በፈጠረው ፍርሃት ምክንያት በሺዎች የሚቆጠሩ የውጭ ሀገር ዜጎች ወደ ሀገራቸው ለመመለስ ቆንስላዎችን እንዲሁም ጊዜያዊ መጠለያዎችን እያጨናነቁ ይገኛሉ።
ባለፉት ሳምንታት በተቀሰቀሰ የፀረ-ስደተኛ ጥቃት የሰዎች ሕይወት መጥፋቱ ስጋቱን ይበልጥ አባብሶታል።
የደቡብ አፍሪካ መንግስት ሊፈጠር የሚችል ሁከትን ለመከላከል ተጨማሪ የፖሊስ ኃይል ያሰማራ ሲሆን ወታደራዊ ኃይሉንም በተጠንቀቅ አቁሟል።
ፕሬዝዳንት ሲሪል ራማፎዛ ህግ የሚጥሱ አካላት ላይ ጥብቅ እርምጃ እንደሚወሰድ አስጠንቅቀዋል።
በደቡብ አፍሪካ እየተባባሰ የመጣውን የፀረ-ስደተኞች ጥላቻ እና እንቅስቃሴ ተከትሎ ጆን አለን የተባለ ማላዊያዊ ስደተኛ ጥቂት ልብሶቹን በቦርሳው ጠቅልሎ፣ ደቡብ አፍሪካዊት ፍቅረኛውን እና የአንድ ዓመት ልጁን በሀዘን ተሰናብቶ ከሀገሪቱ ለመውጣት አውቶቡስ ለመያዝ ተገዷል።
ጆን አሁን ላይ በደርባን ከተማ በሚገኝ ጊዜያዊ መጠለያ ውስጥ ይገኛል።
ህጋዊ ሰነድ የሌላቸው የውጭ ዜጎች በሙሉ ሀገሪቱን ለቀው እንዲወጡ ፀረ-ስደተኛ ቡድኖች ያስቀመጡት መደበኛ ያልሆነ የጊዜ ገደብ (እስከ ዛሬ ጁን 30 ድረስ) ከመጠናቀቁ በፊት ሀገሪቱን ለቀው ለመውጣት ተስፋ በማድረግ ላይ ከሚገኙ በሺዎች የሚቆጠሩ ሌሎች ስደተኞች ጋር ለአራት ቀናት ያህል አውቶቡስ ሲጠብቅ ቆይቷል።
ምንም እንኳን የደቡብ አፍሪካ መንግስት ይህንን የጊዜ ገደብ ባይቀበለውም እና በስደተኞች ላይ የሚደርሰውን ጥቃት ቢያወግዝም፣ ድርጊቱን በቁርጠኝነት ማስቆም ባለመቻሉ ከሌሎች የአፍሪካ ሀገራት እና የሲቪክ ማህበራት ጠንካራ ትችት እየቀረበበት ይገኛል።
በሔኖክ ወ/ገብርኤል
#Southafrica #emigrants #Nigeria #Ethiopia #Ghana
#ጌጡተመስገንሚዲያናኮሙኒኬሽንስ
#Getutemesgenmediacommunications
Source: GetuTemesgen









No comments yet.