የአሜሪካ ምክትል ፕሬዝዳንት ጄዲ ቫንስ ከፎክስ ኒውስ ጋር ባደረጉት ቃል ምልልስ “አሜሪካ ከኢራን ጋር በጣም ጥሩ ነጥብ ላይ እንደምትገኝ” ተናገሩ።
ከኢራን ጋር የሚደረጉ ድርድሮች ስኬታማ ከሆኑ “የተለወጠች ኢራንን ትመለከታላችሁ” ብለዋል።
“በቅርብ ሳምንታት ውስጥ ኢራናውያን መርከብ ላይ ጥቃት አላደረሱም። በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ነዳጅ እያለፈ ነው። ምክንያቱም ኢራናውያን መርከብ ላይ ጥቃት ቢፈጽሙ የአጸፋ ምላሽ እንደሚሰጡ ፕሬዝዳንቱ በግልጽ ተናግረዋል” ሲሉም ገልጸዋል።
ቫንስ በቃለ ምልልሳቸው “ከኢራን ጋር የሚደረጉ ድርድሮች ስኬታማ ከሆኑ፣ ስኬታማ እንዲሆኑም እንፈልጋለን፣ በዘላቂነት የተለወጠች ኢራንን የምትመለከቱ ይሆናል” ብለዋል።
“የተለወጠች” ብለው የገለጿት ኢራን ቀጣናዊ ሽብር እና አለመረጋጋት እንደማትደግፍ እንዲሁም በዘላቂነት የኒውክሌር ፍላጎቷን እንደምትሰርዝ ገልጸዋል።
“በዚህም ምክንያት የዓለም ምጣኔ ሃብት ዳግመኛ ይቀበላታል። ይህም ለአሜሪካውያን እና መላው ቀጣና ጥሩ ውጤት ነው” ብለዋል።
ጄዲ ቫንስ አክለውም “የተገባ ባህሪ ካላሳዩ እና ማየት የምንፈልገውን ለውጥ ካላመጡ የኒውክሌር መርሃ ግብራቸው ይወድማል፤ ወታደራዊ አቅማቸው ይንኮታኮታል። አሜሪካ ከእነሱ አንጻር ጠንካራ ናት” ብለው ተናግረዋል።









No comments yet.