#Ethiopia | የኢሎን መስክ የጠፈር ኩባንያ SpaceX በጥር 2025 ወደ ጨረቃ ያመሩ ሁለት የጨረቃ ማረፊያ መንኮራኩሮችን ካጓጓዘ በኋላ በጠፈር ሲንሳፈፍ የቆየው የFalcon 9 ሮኬት የላይኛው ክፍል ነሐሴ 5 ቀን 2026 ጨረቃን በሰዓት 5,400 ማይል (8,690 ኪሎሜትር) ፍጥነት በመመታት አዲስ ጉድጓድ ፈጥሯል።
ሮኬቱ ተልዕኮውን ካጠናቀቀ በኋላ ነዳጅም ሆነ የመመሪያ ሥርዓት ስላልነበረው ራሱን መቆጣጠር አልቻለም።
በፀሐይ እና በጨረቃ የስበት ኃይሎች ተጽዕኖ ወደ ጨረቃ የሚያመራ መስመር ላይ ገብቶ በEinstein Crater አካባቢ መጋጨቱን ሳይንቲስቶች አስቀድመው ትክክለኛ ትንበያ አድርገው ነበር።
ክስተቱ በቀጥታ በካሜራ ሊቀረጽ ባይችልም፣ በቺሊ የሚገኘው የEuropean Southern Observatory ግዙፍ ቴሌስኮፕ ከግጭቱ በኋላ የሶዲየም እና ሊቲየም ጋዞች የያዘ ግዙፍ የአቧራ ደመና መመዝገቡን አረጋግጧል። ሳይንቲስቶች ሶዲየሙ ከጨረቃ አፈር ሲመነጭ፣ ሊቲየሙ ደግሞ ከሮኬቱ ክፍል ሊሆን እንደሚችል ገልጸዋል።
የአቧራው ደመና ለ5 እስከ 10 ደቂቃዎች ታይቷል። በግጭቱ ምክንያት በጨረቃ ላይ አዲስ ጉድጓድ ተፈጥሯል።
የመጀመሪያ ግምቶች ጉድጓዱ 20 ሜትር (60 ጫማ) ያህል ስፋት ሊኖረው እንደሚችል ሲጠቁሙ፣ ሌሎች ሞዴሎች ግን 40 ሜትር (130 ጫማ) ሊደርስ እንደሚችል ያመለክታሉ። ትክክለኛው መጠን በቅርቡ በጨረቃን ከምህዋር በሚቃኙ መንኮራኩሮች ፎቶ ከተነሳ በኋላ ይረጋገጣል።
ባለሙያዎች ክስተቱ በምድር ወይም በማንኛውም ጠፈርተኛ ላይ ምንም አደጋ እንዳልፈጠረ ቢገልጹም፣ የሰው ሠራሽ ነገሮች በከፍተኛ ፍጥነት ጨረቃን ሲመቱ ምን እንደሚፈጠር ለማጥናት እጅግ የማይደገም የሳይንስ እድል መሆኑን ገልጸዋል። የNASA እና የደቡብ ኮሪያ የጨረቃ መንኮራኩሮች የግጭቱን ቦታ በቅርቡ ፎቶግራፍ ለማንሳት ይሞክራሉ።
ይህ ክስተት የጠፈር ቆሻሻ አስተዳደር እየተባባሰ የመጣ ዓለም አቀፍ ፈተና መሆኑንም እንደገና አሳይቷል። ወደፊት የጨረቃ ተልዕኮዎች እየበዙ ሲሄዱ፣ የተተዉ ሮኬቶችና ሌሎች የጠፈር ቅሪቶች እንዴት እንደሚቆጣጠሩ ትልቅ የፖሊሲ እና የቴክኖሎጂ ጥያቄ እየሆነ መጥቷል።
በዚህ ክስተት አንድ አዲስ ታሪካዊ እውነታ ተመዝግቧል፤ የሰው ልጅ በጨረቃ ላይ የተወው አሻራ የአፖሎ ተልዕኮዎች የእግር አሻራ ብቻ ሳይሆን፣ በሰው ሠራሽ ሮኬት የተፈጠረ አዲስ ጉድጓድም ሆኗል።
Getu Temesgen – (ጌጡ ተመስገን)
Source: GetuTemesgen









No comments yet.