ደንበኞች የቆጣሪ ንባባቸውን በራሳቸው ወደ ሲስተም የሚልኩበት ቴክኖሎጂ በሙከራ ላይ መሆኑ ተገለፀ

- Advertisement -
Sidebar AD

በ2018 በጀት ዓመት የሃይል ብክነትን ለመቀነስ 2.47 ሚሊዮን ቆጣሪዎችን መፈተሹን ያስታወቀው የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ፤ ደንበኞች የቆጣሪ ንባባቸውን በራሳቸው ወደ ሲስተም የሚልኩበት የቴሌግራም መተግበሪያ በሙከራ ላይ እንደሚገኝ አስታውቋል ።

የአገልግሎቱ ዋና ስራ አስፈፃሚ ኢንጂነር ጌቱ ገረመው የ2018 በጀት ዓመት የእቅድ አፈፃፀም እና 2019 እቅድን አስመልክቶ ለመገናኛ ብዙሃን በሰጡት መግለጫ ፤ በተደረገው የቆጣሪ ምርመራ 87 ሺህ 716 የተለያዩ ግኝቶች የተገኙ መሆኑን አንስተዋል ።

ይህም 1 ሺህ 493 ጊጋ ዋት በሰዓት የኢነርጂ ብክነት ወይም 2.89 ቢሊዮን ብር መሆኑን ገልፀዋል ። በተወሰደ የማስተካከያ እርምጃዎም 2.23 ቢሊዮን ብር ለተቋሙ ገቢ መሰብሰቡን አስረድተዋል ።

በተመሳሳይ የሀይል ስርቆት ፈፅመው የተገኙ 1 ሺህ 89 ግለሰቦችን በህግ ተጠያቂ የማድረግ ስራ እየተሰራ መሆኑንም አንስተዋል ።

ተቋሙ በቴክኖሎጂ ዘርፍም 76 ሺህ 940 የደንበኞች ቅሬታዎች ተቀብሎ 71 ሺህ 676 ቅሬታዎችን በመፍታት 93.2 በመቶ አፈፃፀም እንዳስመዘገበ ጠቁመዋል ።

የደንበኞች ግንኙነት ማዕከሉን ወደ አዲስ ስርዓት በማሸጋገር በስልክ፣ በአጭር መልዕክት፣ በፌስቡክ፣ በዋትስአፕ እና በቴሌግራም አገልግሎት መስጠት መጀመሩንም ዋና ስራ አስፈፃሚው አስገንዝበዋል ።

በተጨማሪም ለቅድመ ክፍያና ድህረ ክፍያ ተጠቃሚዎች ኢ-ደረሰኝ ማግኘት የሚያስችል መተግበሪያ ስራ ላይ መዋሉን፣ የሃይል ስርቆትና የመሰረተ ልማት ጉዳት ሪፖርት ለማድረግ የ908 አጭር መልዕክት ስርዓት መጀመሩን ገልጿል ።

ከዚህ ባለፈም ደንበኞች የቆጣሪ ንባባቸውን በራሳቸው ወደ ሲስተም የሚልኩበት ኢኢዩ የቴሌግራም ቦት በሙከራ ላይ መሆኑን እንዲሁም የታቀዱና ያልታቀዱ የሃይል መቆራረጦችን የሚቆጣጠር ሲስተም ወደ ስራ መግባቱን አስታውቋል።

በስነ-ምግባርና ፀረ ሙስና ስራ 621 ጥቆማዎችና አቤቱታዎች መቀበሉን የገለጹት ዋና ስራ አስፈፃሚው ከእነዚህ 595 ላይ ምርመራ በማድረግ ምላሽ መሰጠቱን አንስተዋል ።

በምርመራው ጥፋተኛ ሆነው ከተገኙ 169 ሰራተኞች ውስጥ 166 ላይ የፅሁፍ ማስጠንቀቂያ፣ የደመወዝ ቅጣት፣ ከስራ ቦታ ማንሳትና ስንብትን ጨምሮ የተለያዩ አስተዳደራዊ እርምጃዎች መወሰዳቸውንም አስረድተዋል ።

በመሰረተ ልማትና በንብረት ላይ የስርቆትና የውድመት ባደረሱ 124 ግለሰቦች ላይ ክስ ተመስርቶ እስከ 15 ዓመት ፅኑ እስራት እንዲቀጡ በፍርድ ቤት መወሰኑን አስታውቀዋል ።

#አሐዱ


Source: Yeneta Tube

Comments

No comments yet.

- Advertisement -
Advertisement post bottom2

You might want to listen to: