የኢትዮ ኢስታንቡል ጠቅላላ ሆስፒታል ሜዲካል ዳይሬክተርና ታዋቂ የቀዶ ጥገና ሐኪም ዶ/ር ስዩም ካሣ መርኔ (ተባባሪ ኘሮፌሰር) የኢትዮጵያ ቀዶ ጥገና ማህበር / Surgical Society of Ethiopia/ የ2026 የህይወት ዘመን ስኬት ተሸላሚ ኾኑ።
ዶ/ር ስዩም በኩባ የሕክምና ትምህርታቸውን ካጠናቀቁ በኋላ እኤአ ከ1992 ጀምሮ ላለፉት 33 ዓመታት በዋንኛነት በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የአዲስአበባ ዩኒቨርሲቲ የሕክምና ዲፓርትመንት በመምህርነት፣ በቀዶ ጥገና ሐኪምነት፣ በዲንነት በተጨማሪም በዳግማዊ ሚኒልክ ፣ በጳውሎስ ሆስፒታሎች በደረትና አካባቢው ቀዶ ጥገና ሐኪምነት ማገልገላቸው ታውቋል። በተጨማሪም በተለያዩ የግል ሆስፒታሎች የደረትና አካባቢው ቀዶ ጥገና ሕክምና በማስጀመር ጭምር አገልግለዋል።
ዶ/ር ስዩም ከ30 በላይ ከሙያው ጋር በቀጥታ የተገናኙ ጥናታዊ ጹሑፎችን በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር ታዋቂ ጆርናሎች ላይ አሳትመዋል።
ዶ/ር ስዩም የማኀበሩ 30ኛው ተሸላሚ መሆናቸው ታውቋል።
“ሽልማቱ ምን ስሜት እንደፈጠረባቸው ዶ/ር ስዩም ተጠይቀው የዓመታት ልፋትና ጥረታቸው ዕውቅና ያገኘበት በመኾኑ መደሰታቸውን ተናግረዋል።
ዶ/ር ስዩም ሥራ ሲጀምሩ የደረትና አካባቢው ቀዶ ጥገና ሐኪሞች ቁጥር እሳቸውን ጨምሮ 3 ብቻ እንደነበሩ አስታውሰው በአሁን ሰዓት ግን ተተኪ ወጣቶችን በማስተማር የሐኪሞችን ቁጥርና ሕክምናውንም ለማዘመን በተደረገው ጥረት በአቅማቸው ባደረጉት አስተዋፅኦ ደስተኛ መኾናቸውን ጠቅሰዋል።
ስለኢትዮጵያ ቀዶ ጥገና ማህበር
የኢትዮጵያ ቀዶ ጥገና ማህበር / Surgical Society of Ethiopia / ከተቋቋመ 31 ኛ ዓመት ያስቆጠረ ሲኾን በየዓመቱ ኮንፈረንስ በማካኼድ፤ ከኮንፈረንሱ ጎን ለጎን በሙያው ውስጥ ላቅ ያለ አበርክቶ ላላቸው ባለሙያዎች የዕውቅና ሽልማት ይሰጣል።


Source: FastMereja









No comments yet.